05/08/2025
ህጋዊ እና ደህንነቱ የተጠበቀ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት፤ ለሁለንተናዊ ተጠቃሚነት
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29 ቀን 2017 ዓ.ም፡- ዜጎቻችን በህገ-ወጥና ደህንነቱ ባልተጠበቀ መንገድ ወደ ተለያ ሀገራት ለሥራ ለመሰማራት ሲሞክሩ ለተለያዩ ችግሮች እየተጋለጡ ነው፡፡ ህገ ወጥ ስደት በዜጎቻችን ላይ ከሚያደርሰው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ባሻገር የበርካታ ዜጎቻችንን ውድ ሕይወትም እየቀጠፈ ይገኛል፡፡ ሰሞኑን በጀልባ መስጠም ምክንያት በየመን በዜጎቻችን ላይ የደረሰው ልብ ሰባሪ የሞት አደጋ የዚህ የህገወጥ ስደት አስከፊ ገጽታ ሁነኛ ማሳያ ነው፡፡
መንግስት መሰል ችግሮችን ለመቆጣጠር በሀገር ውስጥ ከሚፈጥረው ሰፊ የሥራ ዕድል በተጨማሪ ወደ ውጭ ሀገራት ሄደው መስራት ለሚፈልጉ ዜጎች ህጋዊና ደህንነቱ የተጠበቀ ስርዓት ለመዘርጋት በልዩ ትኩረት ሲሰራ ቆይቷል፡፡ ስርዓቱ የዜጎችን ክብር እና ደህንነት ብቻ ሳይሆን ፍትሃዊና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ የተቀረፀ ነው፡፡
ከ2014 በጀት ዓመት ጀምሮ ሂደቱ ከሰው እጅ ንክኪ እንዲፀዳና በቴክኖሎጂ እንዲታገዝ በማድረግ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪቱ በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ስርዓት ብቻ ተግባረዊ እየተደረገ ይገኛል፡፡ በዚህም በ2014 በጀት ዓመት 69 ሺህ 718፤ በ2015 በጀት ዓመት 102 ሺህ 076፣ በ2016 በጀት ዓመት 345 ሺህ 167 እንዲሁም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 503 ሺህ 173 ዜጎች መንግስት በዘረጋው ህጋዊ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት ስርዓት ተጠቃሚ መሆን ችለዋል፡፡
መንግስት ዘርፉን ለማዘመንና የዜጎችን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እያደረገ ባለው ጥረት ለውጭ ሀገር ሥራ ስምሪቱ ዜጎችን በልዩ ሁኔታ ለማዘጋጀት የሚያስችል ስርዓተ ስልጠና ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል፡፡ የስልጠና ተደራሽነቱንና ፍትሃዊነቱንም ለማረጋገጥ ከመንግስት ተቋማት ባሻገር የግል ማሰልጠኛ ተቋማት በሥራው ውስጥ እንዲገቡ ተደርጓል፡፡
የመዳረሻ ሀገራትን ለማስፋት በተደረገው ጥረትም ከሳዑዲ አረቢያ፣ ከተባበሩት አረብ ኤሚሬት፣ ከዮርዳኖስ፣ ከሊባኖስ፣ ከኳታር እና ከኪዌት መንግስት ጋር የሁለትዮሽ የሥራ ስምሪት ስምምነት በመፈራረም ወደ ሥራ እንዲገባ ተደርጓል፡፡
ይህም ዜጎቻችን በእነዚህ ሀገራት መብትና ደህንታቸው እንዲሁም ተጠቃሚነታቸው ተጠብቆ እንዲሠሩ ዕድል ተፈጥሯል፡፡ በቀጣይም ሚኒስቴር መስሪያ ቤታችን ከሚመለከታቸው ባለድርሻና አስፈፃሚ አካላት ጋር በመሆን የመዳረሻ ሀገራትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማላቅ በልየ ትኩረት የሚሰራውን ሥራ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡
በአንፃሩ ሕገ-ወጥ አዘዋዋሪዎች በአሳሳች መረጃ እና በአማላይ ማስታወቂያ አሁንም ዜጎቻችንን ለከፋ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ቀውስ መዳረጉን ቀጥለዋል፡፡ ስለሆነም ዜጎች ህጋዊ እና ደህንነቱ የተጠበቀ የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪትን ብቻ ምርጫቸውን በማድረግ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ካላስፈላጊ ወጪና እንግልት እንዲታደጉ ጥሪ እያቀረብን በየአካባቢው የሚያስተዋሉትን የህገወጥ አዘዋዋሪዎች እንቅስቃሴ በአቅራቢያቸው ለሚገኙ የሕግ አስከባሪ አካላት እንዲያሳውቁ በጥብቅ እናሳስባለን፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር