03/10/2024
23/01/2017
ዜና EOEAF
የኢትዮጵያ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት አገናኝ ኤጀንሲዎች አሰሪ ፌዴሬሽን የዜጎችን መብት ለማስከበር ከኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ጋር የጋራ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ፡፡
የኢትዮጵያ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት አገናኝ ኤጀንሲዎች አሰሪ ፌዴሬሽን ከኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን በውጭ ሀገር በስራ የሚሰማሩ ዜጎችን መብት እና ደህንነት ለማስጠበቅ ከዚህ ቀደም በጋራ አብሮ ለመስራት በመርህ ደረጃ ንግግር ሲያደርግ የነበረ ሲሆን ዕለተ ሀሙስ መስከረም 2017 በኢትዮጵያ የሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን መሰብሰቢያ አዳራሽ ከሁለቱም በኩል የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የአለም አቀፉ የሥራ ድርጅት ተወካይ፣ የተለያዩ የሚድያ ተቋማት እና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል፡፡
የኢትዮጵያ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት አገናኝ ኤጀንሲዎች አሰሪዎች ፌዴሬሽን ፕሬዝደንት አቶ ነቢል መሀመድ በመክፈቻ ንግግራቸው ፌዴሬሽኑ በውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት በስራ የሚሰማሩ ዜጎች መብት፣ ክብር እና ደህንነት እንዲጠበቅ ለኤጀንሲዎች ከመንግስትና ከአለም አቀፉ የሥራ ድርጅት (ILO) ጋር በመተባበር በርካታ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች መሰጠታቸውን ጠቅሰው በተለይ ፌዴሬሽኑ ከእነኝሁ የባለድርሻ አካላት ጋር የስነምግባር ደንብ አዘጋጅቶ እና አፀድቆ ኤጀንሲዎች ህግን፣ ዘርፉን በተመለከተ የወጣውን አዋጅ እና አለም አቀፍ መርሆዎችን በጠበቀ መልኩ ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን አስገንዝበዋል፡፡ ፕሬዝደንቱ አክለውም ፌዴሬሽኑ በዋናነት የአባላቶቹን መብት ከማስከበር ባሻገር የዜጎች መብት፣ ጥቅም እና ደህንነት እንዲከበር የሚሰራ መሆኑን ጠቅሰው ከኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ጋር በዛሬው ዕለት የተፈረመው የመግባቢያ ሰነድም የዜጎችን መብት በማስከበር ረገድ ጉልህ ሚና የሚጫወት መሆኑን ገልፀዋል፡፡
በመቀጠል ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ የሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ፕሬዝደንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ኮንፌዴሬሽኑ ለዜጎች የሰብዓዊ መብት መከበር ከሚሰራ ከየትኛውም ተቋም ጋር በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውን ጠቅሰው ከኢትዮጵያ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት አገናኝ ኤጀንሲዎች ፌዴሬሽን ጋር በጋራ ለመስራት በርካታ ጥረት ሲደረግ የነበረ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡ አክለውም ፕሬዝዳንቱ ይህ የመግባቢያ ሰነድ ወደ ትግበራ ሲገባ በውጭ ሀገር ስራ ስምሪት የሚሰማሩ ዜጎች ከምልመላ ጀምሮ እስከሚሄዱበት የመዳረሻ ሀገራት እና ቆይታቸው ላይ በጋራ በሚመሰረተው የቅጥር እና የምልመላ አማካሪ ኮሚቴ (Migrant Workers Recruitment Advisory Committee) አማካኝነት መረጃዎችን በመሰብሰብ እና ልውውጥ በማድረግ የዜጎችን መብት ለማስከበር ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ገልፀዋል፡፡ ፕሬዝደንቱ ከኢትዮጵያ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት አገናኝ ኤጀንሲዎች አሰሪ ፌዴሬሽን ጋር በጋራ መስራታቸው በርካታ ዜጎች ህጋዊ በሆነ መንገድ እንዲሰማሩ ከማገዝ በተጨማሪ ዜጎች ላይ የተለያዩ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እንዳይፈፀምባቸው መረጃዎችን ለመለዋወጥ የሚያስችል መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
የመግባቢያ ሰንዱ ላይ በተቀመጠው መሰረት ጥምር ኮሚቴ በመመስረት እና የጋራ አክሽን ፕላን በማውጣት ወደ ውጭ ሀገር በሥራ የሚሰማሩ ዜጎችን መብት ለማስከበር በርካታ ስራዎች እንደሚሰራ ይጠበቃል፡፡